ኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ዘርፍ ከአፍሪካ ሁለተኛ ሆነች
የኢንቨስትመንት ኮሚሽነር አቶ ዘለቀ ተመስገን “ኢትዮጵያ፡ አዲሱ የኢንቨስትመንት መዳረሻ” በሚል ርዕስ ባደረጉት የፓናል ውይይት ላይ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሁለተኛው በጣም ማራኪ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መዳረሻ እንደሆነች እና ቻይናም ለምስራቅ አፍሪካዊቷ ሀገር ግንባር ቀደም የኢንቨስትመንት አጋር ሆና መቀጠሏን ተናግረዋል።
ኮሚሽነሩም ኢትዮጵያ ከግብፅ በመቀጠል በአፍሪካ ሁለተኛዋ ከፍተኛ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት (FDI) መዳረሻ በመሆን ባለፉት አምስት ዓመታት በአጠቃላይ 18.6 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ስባለች ብለዋል። ይህም የቻይና ኩባንያዎች በአገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ ኢንቨስት በማድረግ በሐምሌ 7፣ 2025 በተጠናቀቀው የኢትዮጵያ የበጀት ዓመት 4 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ያስመዘገበች ሲሆን ገቢውም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር 22.7 በመቶ ጭማሪ እንዳሳየ ኮሚሽነሩ ተናግረዋል።
ኮሚሽነሩም የውጭ ዜጎች በአገሪቱ ውስጥ የመኖሪያ ቤቶችን በሕጋዊ መንገድ እንዲይዙ መፈቀዱ እና የውጭ ኢንቨስትመንት ፖሊሲ ወደ ክፍት የኢንቨስትመንት ፖሊሲ በመቀየር የውጭ ባለሀብቶች ቀደም ሲል የተገደቡባቸው እንደ ኤክስፖርት፣ አስመጪ፣ የችርቻሮ እና የጅምላ ንግዶች ባሉ ቁልፍ የኢንቨስትመንት ዘርፎች እንዲሳተፉ መደረጉ ትልቅ ተጽዕኖ ፈጥሯልም ብለዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ባለፉት አምስት ዓመታት ለውጭ ዜጎች 1477 አዳዲስ የኢንቨስትመንት ፈቃዶችን እንዳወጣ ጠቅሰዋል።
ቀጥሎም የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር አቶ ካሳሁን ጎፌ የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ አቀማመጥ፣ ትልቅ እና ወጣት የሰው ኃይል እና የኢንቨስትመንት የአየር ንብረት መሻሻል አገሪቱን በአፍሪካ ውስጥ ለኢንቨስትመንት ተወዳዳሪ ማዕከል እንዳደረጋት እና መንግስትም የኢንቨስትመንት ሁኔታን ለማሻሻል የታለሙ ተከታታይ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ማድረጉ ይህም ቁልፍ ዘርፎችን ለውጭ ባለሀብቶች መክፈቱ እና የግል ንግዶችን ሚና ማስፋቱ ትልቅ ለውጥ አንዳመጣ ተናግረዋል።
ሚኒስቴሩም ኢትዮጵያ በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና (AfCFTA) ውስጥ መሳተፏ አዳዲስ በሮችን እየከፈተላት እና ወደ አህጉራዊ ገበያ እንድትገባ እያግዛት እንደሆነ እና መንግስትም በአሁኑ ወቅት ሰፊውን የገበያ ዕድል የበለጠ ለመጠቀም የኢንቨስትመንት ፕሮቶኮልን ተግባራዊ ለማድረግ እየሰራ እንደሆነ አክለዋል።
በተባበሩት መንግስታት የንግድ እና ልማት ኮንፈረንስ መሠረት ቻይና ጉልህ ባለሀብት እንደሆነች የሚታወቅ ሲሆን በኢትዮጵያ ውስጥም በማኑፋክቸሪንግ እና በአገልግሎት ዘርፎች ከፍተኛ ኢንቨስት በማድረግ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ውስጥ 60 በመቶውን ታስመዘግባለች። በኢትዮጵያ ውስጥ ሌሎች ዋና ዋና የኢንቨስትመንት አጋሮችም ሳውዲ አረቢያ እና ቱርክ ይገኙበታል።