የጉምሩክ ኮሚሽን የተያዙ እቃዎችን ለበጎ አድራጎት ድርጅቶች የመለገስ ልምዱን ሊያቆም ነው ተባለ
የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን የተያዙ የኮንትሮባንድ ዕቃዎችን ለበጎ አድራጎት ድርጅቶች የመለገስ የረዥም ጊዜ ልምዱን ሊያቆም ነው ተባለ። ለውጡ የጉምሩክ አዋጅ ማሻሻያ ረቂቅ ማዕከላዊ አካል በመሆን የኢትዮጵያን የንግድ እና የፋይናንስ አሠራር ከፌዴራል እና ከዓለም አቀፍ ደረጃዎች ጋር ለማጣጣም፣ በአስመጪዎች ላይ የሚደርሰውን የአሠራር ጫና ለማቃለል እና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመጣው የኮንትሮባንድ ንግድ ላይ አፈጻጸምን ለማጠናከር የሚደረገውን ጥረት የሚደግፍ ነው ተብሏል።
ኮሚሽኑም ኮንትሮባንድ ውስብስብ እየሆነ መምጣቱን ገልፀው ሕገወጥ አዘዋዋሪዎች በአሁኑ ጊዜ ከፍተኛ አቅም ያላቸው እና የተደበቁ ክፍሎች እንዲሁም ጥይት መከላከያ ጎማዎች ያላቸው ተሽከርካሪዎችን በማሰማራት አሁን ካለው የማስፈጸሚያ ዘዴዎች ስለሚበልጡ በታቀደው ለውጥ መሰረት እነዚያ እቃዎች ተሽጠዉ በገንዘብ ሚኒስቴር ቁጥጥር ስር ገቢው ወደ ኮሚሽኑ ተመልሶ ኮንትሮባንድን ለመዋጋት እራሱን የሚያጠናክር የገንዘብ ፍሰት ይፈጥራልም ብለዋል።
በተጨማሪም ኮሚሽኑም በርካታ ነባር ድንጋጌዎች ጊዜ ያለፈባቸው እና በዓለም የጉምሩክ ድርጅት (WCO) እና የዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) ከተቀመጡት መመዘኛዎች በታች መሆናቸውን ጠቁመዉ ፣ ይህም በፍጥነት እየሰፋ ለሚሄደው የማኑፋክቸሪንግ መሠረት እና ግልጽነትን ለሚፈልግ የኢንቨስትመንት ሁኔታ ገደብ ይጥላልም ብለዋል።
ኮሚሽኑም የባህር እና የየብስ ጭነት ለጉምሩክ ሂደት አንድ ወር ከ15 ቀን የአየር ጭነት ክሊራንስ ደግሞ ከ10 ቀን ጀምሮ እስከ አንድ ወር ሙሉ እንደሚደርስ ገልፀው የነባር ቀነ-ገደቦች ትክክለኛ የሂደት ጊዜዎችን ማንጸባረቅ ባለመቻላቸው ሰፊ አለመታዘዝን ፈጥሯልም ብለዋል። በዚህም ምክንያት በረቂቁ ስር ንግዶች ለጭነት ማጽጃ የተራዘመ የጊዜ ሰሌዳዎችን ያያሉ ተብሏል። ረቂቁም ሁሉንም ቀረጥ እና ታክሶችን ወዲያውኑ መክፈል ለማይችሉ አስመጪዎች እቃዎቻቸው በከፊል እንዲለቀቁ በመፍቀድ የሎጂስቲክስ ጫናዎችን ለማርገብ እና የአቅርቦት ሰንሰለት ቀጣይነትን ለመደገፍ ይረዳልም ተብሏል።
ከምንዛሬ ውጣ ውረድ ጋር ተያይዞ የሚደርሰውን የገቢ ብክነት ለመከላከል ለቀረጥ የሚውለው የውጭ ምንዛሪ ዋጋ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ መግለጫ ከተመዘገበበት ቀን ይልቅ ተቀባይነት ባለው ቀን ወደተቀመጠው ዋጋ ይሸጋገራልም ተብሏል። ሌሎች ማስተካከያዎች በመነሻ መለያ አሰጣጥ ላይ ፣ የተትረፈረፈ ክፍያ የተመላሽ ገንዘብ ሂደቶች ላይ እና ለታማኝ ነጋዴዎች እና ለተፈቀዱ የኢኮኖሚ ኦፕሬተሮች ተለዋዋጭ የዋስትና ዝግጅቶች ላይም ያተኩራል ተብሏል።
በገዢ እና በሻጭ መካከል ያለው የግብይት ዋጋ ለግብር ስሌት እንደ ዋና መሠረት ሆኖ የሚያገለግል ሲሆን፣ የጉምሩክ ባለሥልጣን የታወጁ እሴቶች አጠራጣሪ ናቸው ከተባለ ተጨማሪ ሰነዶችን የመጠየቅ ስልጣንም ተሰጥቶታል ተብሏል። አዲስ የግምገማ ዳታቤዝም የአደጋ ግምገማ እና የዋጋ ማረጋገጫን በመደገፍ፣ ከአስመጪዎች የግምገማ አሠራሮች ወጥነት ባለማሳየታቸው ምክንያት ለረጅም ጊዜ የቆዩ ቅሬታዎችን ለመፍታት ያስችላልም ተብሏል።
ኮሚሽኑም አሁን ያለው ቅጣቶች በቂ ስላልሆኑ እና የኮንትሮባንድ ነጋዴዎች ቅጣቶችን እንደ ንግድ ሥራ ዋጋ እንዲወስዱ ስላስቻለ ቅጣቶች የበለጠ ጥብቅ እንዲሆኑ አስቀምጧል። ሸቀጦችን ለመደበቅ የተሻሻሉ ወይም የኮንትሮባንድ ዕቃዎችን ሲያጓጉዙ የተገኙ ተሸከርካሪዎች ሊወረሱ እንደሚችሉ ገልጾ ቀደም ሲል የወጣውን ድንጋጌ በመቀየር በአንዳንድ ሁኔታዎች 100,000 ብር ቅጣት እንደሚያስቀጣ ገልጿል።